ሚሚ ስብሃቱ ጠረጴዛ ምን ያደርግላታል?

ከዳዊት ሰለሞን

ጠረጴዛ ከመመገቢያነት፣ለመጻፊያ ማስደገፊያነትና ከቁሳቁስ ማስቀመጫነት በተጨማሪ በዙሪያው በሚኮለኮሉት ወንበሮች የተነሳ ሰዎችን በአንድነት መሰብሰብ በመቻሉ የሐሳብ መንሸራሸሪያ መድረክ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡በጠረጴዛ ዙሪያ የሚቀመጡ ግለሰቦችና ቡድኖች በፊት ለፊታቸው በተዘረጋው ጠረጴዛ ላይ ሐሳባቸውን…..አመለካከታቸውንና አይዶሎጂያቸውን ያቀርባሉ፡፡የተጣሉ፣ልዩነት ያለባቸው ወገኖችም በጠረጴዛ ዙሪያ ቅራኔያቸውን ለማጥበብ ይደራደራሉ፡፡
ሚሚ ስብሃቱ ከቪኦኤ መልስ በታደለችው ዛሚ ራዲዩ ጣቢያ አማካኝነት ‹‹የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ››የተባለ መርሃ ግብር ታዘጋጃለች፡፡በሚሚ ጠረጴዛ ዙሪያ እንዲታደሙ የሚፈቀድላቸው ወይም በቋሚነት በመሳተፍ ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞች ጋዜጠኝነታቸው‹‹በጠረጴዛው››የተወሰነ መሆኑም ድንቅ ይለኛል፡፡
ጋዜጠኞቹ ሚሚ ስታሽካካ አብረዋት የሚያሽካኩ የራሳቸው ሳቅ ወይም ለቅሶ የሌላቸው ‹‹እንገላበጥ››በማለት የሚጠይቁ ሁሌም ባለችው ላይ የሚጨምሩ መሆናቸውም ‹‹ጠረጴዛው››እውነት ከብበውታልን በማለት እንድጠይቅ ያደርገኛል፡፡
ሚሚ ዳዊት ከበደ መታሰር ይገባዋል ካለች ቀሪዎቹ የጠረጴዛው ታዳሚዎች‹‹እስካሁን አለመታሰሩ እንደሚገርማቸው ያክላሉ፣አንድነት ፓርቲ የግንቦት 7 ትርፍራፊን ለማግኘት ይሰራል ካለች አጃቢዎቿ ‹‹ለዚህ እኮ ነው የጸረ ሽብር አዋጁ ይሰረዝ የሚለው ይላሉ፡፡
ዛሬ አንድ ወዳጄ ደውሎ ሚሚን ስማት አለኝ፡፡ወሪያቸው ሚስ አና ጎሜዝን የተመለከተ ነበር ፡፡ሚሚ የስድብ መዝገበ ቃላቷን ጠረጴዛዋ ላይ ከፍታ ፖርቹጋላዊቷን የሰብዓዊ መብት ታጋይና የአውሮፓ ፓርላማ አባል ታወርድባታለች፡፡አና ሚሚን ባትሰማትም ሚሚ በተሳደበች ቁጥር ማንነቷን የምትገኝበትን ስብዕና የበለጠ እመለከት ነበር፡፡ማን ነበር ሰው አፉን ሲከፍት ሆዱ ይታያል ያለው፡፡
ሚሚ አና ጎሜዝ ወደ አገራችን እንድትገባ በመደረጓ ብዙ ኢትዮጵያዊያን አዝነዋል፡፡ብላለች የእርሷ ብዙ ስንት እንደሆነ ባይገባኝም፡፡አና ለሚዲያዎች በሰጧቸው ቃለ ምልልሶች መለስን መረር ባሉ ቃላቶች መግለጻቸው ሚሚን አንጨርጭሯታል፡፡እንዲህ በመናገሯ ብዙ ኢትዮጵያዊያን ተቆጥተዋል ከማለትም አልተመለሰችም ‹‹መለስ መላጣ ብሎ ማንም ሊሰድበኝ ይችላል መላጣዬን ግን እንዲነካ አልፈቅድለትም››ማለታቸውን ሚሚ እንዴት እንደረሳቸው አልገባኝም፡፡አና መለስን ‹‹አጭበርባሪ ነበር››በማለት ገልጸውታል፡፡አያጭበረብርም የሚል ካለ አናን መሞገት እንጂ‹‹እንዴት ብሎ በጠረጴዛ ዙሪያ የስድብ መዓት ማዝነብ የሚቻል አይመስለኝም ፡፡
አና መለስን እንዲህ ያሉት ከመሬት ተነስተው አልነበረም፡፡ያው ምርጫ 2005ን ማስታወስ ብቻ ይበቃል፡፡እነ ሚሚ የመለስን የቲና ተርነር ዘፈን በማስታወስም ወይዘሮዋ ብርሃኑ ነጋ ጋር ስለነበራቸው ግኑኝነት ለመሳለቅ ሞክረዋል፡፡እንግዲህ አና በዘንድሮው የአዲስ አበባ አመጣጣቸው ደመቅ ያሉ ፎቶ ግራፎችን ከአባ ዱላ ገመደና ከተሾመ ቶጋ ጋር ተነስተው ተመልክተናል፡፡አና አባዱላን ወይም ተሾመን አፈቀሩ ወይስ ሁለቱ ሰዎች አናን ከብርሃኑ ነጠቁ?
እነሚሚ ይህንን ሊያነሱ አልቻሉም፡፡ከዚህ ይልቅ ተዘባዝበው አድማጮቻቸውን ተሰናበቱ፡፡እኔ ልጠይቅ በዛሚ ጠረጴዛ የሚሰባሰቡ ሰዎች አንድ አይነት ዘፈን የሚዘፍኑ ሚሚ ያለችውን እንደ በቀቀን የሚደግሙ እንደ ገደል ማሚቱ የሚያስተጋቡ ናቸው፡፡ታዲያ ጠረጴዛ ምን ያደርግላቸዋል፡፡ባዶ ቤት አይሻልም፡፡ለእስክስታውም ይመቻል ብዬ እኮ ነው፡፡

zehabesh

Posted on December 8, 2013, in Andinet, Andinet party, ETHIOPIA AMHARIC, Ginbot 7, OLF, oromo and tagged , , . Bookmark the permalink. Leave a comment.

Leave a comment