የሕግ ባለሙያዎች ታሪክና ግዜ የጣሉባችሁን ኃላፊነት እንደምትወጡ ይጠበቃል! [በላይነህ አባተ]

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com)

justiceታሪክና ግዜ በትውልድ ኃላፊነትን ይጥላል፡፡ ይህ ትውልድ በሮማውያን ዘመን ኃላፊነቱን በሚገባ እንደተወጣው ትውልድ ታሪክና ግዜ ኃላፊነት ጥለውበታል፡፡የሮማውያንን ተደጋጋሚ ጪፍጨፋ አያት ቅደመ-አያቶቻችን በሚያስደንቅ ጀብዱ መክተውታል፡፡ ከሮማውያን ቅኝ ገዥዎች ጪፍጨፋ በከፋ ሁኔታ በእጅ አዙር ቅኝ ገዥ አገልጋዮች ህጻናት ጭንቅላታቸውን በላውንቸር እንደሚበረቀሱ፣ እግራቸውን በባሩድ እንደሚቆረጡና ሆዳቸውን እንደሚዘረገፉ አምባ ጊዮርጊስ በዚች ቅጽበት አስገንዝቦናል፡፡ እነዚህን የእጅ አዙር ቅኝ ገዥ አገልጋይ ጨፍጫፊ ባንዳዎችም ሕዝብ ግብግብ ገጥሟቸው ይገኛል፡፡ ይህ የጪፍጨፋ ግዜ ከገዳዮች የወገነውን እርጉሞችና ድምጣችንን አጥፍተን እንጀራችንን የምናሳድደውን አድርባዮች በትዝብት ቴሌስኮፕ ይመለከተናል፡፡

በመላ አገሪቱ በአረመኔዎች እሚፈጸመው የሕዝብ ጪፍጨፋ በደመነፍስ የሚንቀሳቀሱ አውሬዎች እንኳ በሰው እማይፈጽሙት ጪፍጨፋ ነው፡፡ ይህንን ጪፍጨፋ የሚፈጽሙትን አረመኔዎች ከፍርድ ለማቅረብ እናንተ የሕግ ባለሙያዎች የመሪነቱን ሥፍራ እንድትይዙ ግዜና ታሪክ አደራ ጥለውባችኋል፡፡ ሕግ የተሰራው ህሊናውና እምነቱ ያላሰረውን መረን ለማሰር ይመስለኛል፡፡ ህሊናውና እምነቱ ያላሰረው መረኑ ኃይለ-ሰይጣን ደሳለኝ ዛሩን አውርሶ ከወንበር ጎልትቶት እንዳለፈው ሰይጣን በሕዝባችን የጪፍጨፋ አዋጅ አውጇል፡፡ ኃይለ-ሰይጣ ደሳለኝንና የጪፍጨፋ አዋጁን እንዲያውጅ ያዘዙትን አረመኔዎች ከፍርድ እንድታቀርቡ ታሪክ፣ ግዜና ሕዝብ በእናንተ በሕግ ባለሙያዎች ኃላፊነት ጥለዋል፡፡ ይህንን የሕዝብ፣ የታሪክና የግዜ ኃላፊነት ያልተወጣ ዜጋና የሕግ ባለሙያ በሞቱት አጽም፣ ከሞት በተረፉት ዜጎች፣ በመጪው ትውልድ፣ በታሪክና በእግዚአብሔር ሲጠየቅና ሲወቀስ ይኖራል፡፡

የሕግ ባለሙያዎች ሆይ! ጠበቃ፣ ዳኛ፣ አቃቤ ሕግ፣ ሚኒስቴር፣ ፕሮፌሰር፣ ወዘተርፈ ሆናችሁ የምታግበሰብሱት ገንዘብ፣ የምትነዱት መኪና፣ የምትኖሩበት ቪላ በማታውቁት ሰዓት ሞት ሲጠልፋችሁ ተከትሏችሁ አይሄድም፡፡ ታሪክ፣ ትውልድና እግዚአብሔር ግን እየተከተሉ እስከ ዓለም ፍፃሜ ሲወቅሷችሁ ይኖራሉ፡፡ ባልጠበቃችሁት መንገድ አፈር ለሚሆነው ገላችሁ ሳስታችሁ የሕዝብን ጪፍጨፋና የፍትህን መታረድ አግዛችሁ ወይም ችላ ብላችሁ እንደ በፊቱ ባንዳዎችና አድርባዮች የራሳችሁንና የልጅ-ልጆቻችሁን ቅልብ በታሪክና በትውልድ ወቀሳ ሲሸማቀቅ ከመኖር አድኑ፡፡ በህሊናውና በእምነቱ እሚገዛውን ሕዝባችንን የሚጨፈጭፉትን አረመኔዎች ለሕግ አቅርቡ፡፡ ህሊናና ሕግ ቀርቶ ደመነፍስም በማያስራቸው ጭራቆች እንደ ዓባይ እሚፈሰው የንጹሐን ደም የችሎት ያለህ፣ የፍትህ ያለህ፣ የጠበቃ ያለህ፣ የዳኛ ያለህ ሲል ይጮሃል፡፡

የሕግ ባለሙያዎች ሆይ! የንጹሐን ደም ጩኸት፣ ታሪክና ግዜ የጣሉባችሁን ሐላፊነት እንደምትወጡ ይጠበቃል፡፡ አመሰግናለሁ፡፡

 

ነሐሴ ሁለት ሺ ስምንት ዓ.ም

Posted on September 3, 2016, in Andinet, Andinet party, esat.com, ETHIOPIA AMHARIC, Ginbot 7, OLF, oromo. Bookmark the permalink. Leave a comment.

Leave a comment